
በትምራን አዘጋጅነት ለሁለት ቀናት የሚቆይ የሴቶች የሰላም መድረክ የካቲት 01 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ በጋምቤላ ከተማ በመካሄድ ላይ ይገኛል።
መድረኩን በንግግር የከፈቱት የትምራን ባልደረባ አቶ ሮቤል አበበ፣ ትምራን ኢትዮጵያውያን ሴቶች በማንኛውም ፖለቲካዊ፣ ማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ መዋቅሮች ውስጥ እኩል ተሳታፊ የመሆን መብታቸውን እውን እንዲሆን እንዲሁም በአመራር ሰጭነት ሚናቸው እና አቅማቸው እንዲጎለብት የምትሠራ መሆኑን ተናግረዋል።
አቶ ሮቤል በጋምቤላ ከተማ በመካሄድ ላይ ያለው ውይይት የሴቶችን ተሳትፎ የሚያጎላ ለውጥ ለማምጣት ያለመ መሆኑንና ትልቅ ትርጉም ያለው መሆኑን ጠቅሰዋል። የክልሉ ሴቶች በሰላም ግንባታ ላይ ያሉ ችግሮችንና ሴቶች በሰላም ግንባታ ውስጥ ሊሳተፉ የሚችሉባቸው ሁኔታዎች ላይ ሐሳብ እንዲሰጡ ጠይቀዋል።
የሰላም መድረኩ ተሳታፊዎች በኢትዮ ቲንክ ታንክ ግሩፕ አሠልጣኞች አስተባባሪነት በሰላም መፍጠር እና ሰላም መገንባት መካከል ስላለው ልዩነት እና አንድነት፣ ዘላቂ የሰላም ግንባታ እንዲሁም ሴትነት እና ሰላም በሚሉ ጭብጦች ላይ ውይይት አካሂደዋል።
ትምራን ሴቶች በፖለቲካዊ እና በማንኛውም ሕዝባዊ አስተዳደር ጉዳዮች ላይ ጉልህ ተሳትፎ በማድረግ ውሳኔ ሰጪ የሆኑባት አትዮጵያን ማየት የሚል ራእይ አንግባ የምትንቀሳቀስ ሀገር በቀል የተመዘገበች የሲቪክ ማኅበር ነች።